unfoldingWord 08 - እግዚአብሔር ዮሴፍንና ቤተ ሰቡን አዳነ
Esquema: Genesis 37-50
Número de guión: 1208
Lingua: Amharic
Público: General
Finalidade: Evangelism; Teaching
Features: Bible Stories; Paraphrase Scripture
Estado: Approved
Os guións son pautas básicas para a tradución e a gravación noutros idiomas. Deben adaptarse segundo sexa necesario para facelos comprensibles e relevantes para cada cultura e lingua diferentes. Algúns termos e conceptos utilizados poden necesitar máis explicación ou mesmo substituírse ou omitirse por completo.
Texto de guión
ከብዙ ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ባረጀ ጊዜ የከብቶቹን መንጋ የሚጠብቁት ወንድሞቹ እንዴት እንዳሉ እንዲያያቸው የሚወደው ልጁን ዮሴፍን ላከው።
አባታቸው ያዕቆብ ዮሴፍን ከወንድሞቹ ሁሉ አብዝቶ ይወድደው ስለ ነበረና አለቃቸው እንደሚሆን ሕልም አልሞ ስለ ነበር የዮሴፍ ወንድሞች ጠሉት። ዮሴፍም ወደ ወንድሞቹ በመጣ ጊዜ ጠልፈውት ለባሪያ ነጋዴዎች ሸጡት።
የዮሴፍ ወንድሞች ወደ ቤት ከመመለሳቸው በፊት የዮሴፍን ቀሚስ ቀድደው በፍየል ደም ነከሩት። ከዚያም በደም የተነከረውን የዮሴፍን ቀሚስ ለአባታቸው አሳዩት። እርሱም የዱር አውሬ ዮሴፍን ገድሎታል ሲል አሰበ፤ ያዕቆብም በጣም አዘነ።
የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ወደ ግብፅ ወሰዱት። በዚያን ጊዜ ግብፅ በአባይ ወንዝ አጠገብ የምትገኝ ታላቅና ኃያል አገር ነበረች። የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ባርያ አድርገው ለሀብታም የመንግሥት ባለ ሥልጣን ሸጡት። ዮሴፍ ጌታውን በደንብ አድርጎ አገለገለው። እግዚአብሔርም ዮሴፍን ባረከው።
የጌታው ሚስት ከዮሴፍ ጋር ለመተኛት ሞከረች። ዮሴፍ ግን በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት አልሠራም ሲል እምቢ አላት። እሷም ስለ ተናደደችበት በሐሰት ከስሳው ተይዞ ወደ እሥር ቤት ተወሰደ በእሥር ቤትም ቢሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ ሆኖ ስለ ተገኘ እግዚአብሔር ባረከው።
ምንም እንኳ ዮሴፍ ንጹሕ ሰው ቢሆንም ከሁለት ዓመት በኋላ አሁንም በእሥር ቤት ነበር። አንድ ሌሊት ግብፃውያን ‘ንጉሣችን’ የሚሉት ፈርዖን በጣም የታወከባቸውን ሁለት ሕልሞች አለመ። ከአማካሪዎቹ አንዳቸውም የሕልሙን ትርጕም ሊነግሩት አልቻሉም።
እግዚአብሔር ለዮሴፍ ሕልም የመተርጐም ችሎታ ሰጥቶት ነበር፤ ስለዚህ ፈርዖን ዮሴፍን ከእሥር ቤት ወደ ራሱ አስመጣው። ዮሴፍ ሕልሙን ተረጐመለትና እንዲህ አለው። “እግዚአብሔር ሰባት የጥጋብ ዓመታትን ይልካል፣ ቀጥሎም ሰባት የረሀብ ዓመታት ይሆናሉ” አለ።
ፈርዖንም በዮሴፍ በጣም ተገረመ፣ በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ከእርሱ ቀጥሎ ሁለተኛ ባለ ሥልጣን አድርጎ ሾመው።
ዮሴፍም ሕዝቡን በሰባቱ የመልካም ምርት ዓመታት በርካታ እህል በጎተራው እንዲያከማቹ ነገራቸው። የሰባቱ የረሀብ ዓመታት በመጡ ጊዜ ዮሴፍ ከጎተራው ለሕዝቡ እህል በመሸጡ በቂ የሚበላ ምግብ አገኙ።
የረሀቡ አስከፊነት በግብፅ ብቻ ሳይሆን፣ ያዕቆብና ቤተ ሰቡ በሚኖሩበት በከነዓን ምድር ደግሞ ነበር።
ያዕቆብ ልጆቹ እህል እንዲሸምቱ ወደ ግብፅ ላካቸው። የዮሴፍ ወንድሞች ለእህል ሸመታ ሄደው ፊቱ በቆሙ ጊዜ ዮሴፍ መሆኑን አላስተዋሉትም ዮሴፍ ግን አውቋቸዋል።
ዮሴፍ ወንድሞቹን ከፈተናቸው በኋላ ተለውጠው እንደ ሆነ ለማየት እንዲህ አላቸው፣ “አትፍሩ እኔ ወንድማችሁ ዮሴፍ ነኝ ለባርነት ስትሸጡኝ ክፉ ልታደርጉብኝ ሞከራችሁ ነገር ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለመልካም አደረገው መጥታችሁ በግብፅ ኑሩ እኔም ለእናንተና ለቤተ ሰቦቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን አቀርብላችኋለሁ።”
የዮሴፍ ወንድሞች ወደአገራቸው ተመልሰው ዮሴፍ በሕይወት መኖሩን ለአባታቸውለያዕቆብ በነገሩት ጊዜ ያዕቆብበጣም ደስ አለው።
ምንም እንኳ ያዕቆብ ሽማግሌ ቢሆንም ከመላው ቤተሰቡ ጋር ወደ ግብፅ ሄዶ በዚያ ኖሩ። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ልጆቹን እያንዳንዳቸውን ባረካቸው።
እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባቸው የቃል ኪዳን ተስፋዎች ወደ ይስሐቅ ተላለፉ፤ ከዚያም ወደ ያዕቆብ፣ ቀጥሎም ወደ ዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆቹና ቤተ ሰቦቻቸው ተላለፈ። የዐሥራ ሁለቱ ልጆች ዘሮቻቸው ዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ሆኑ።